ጎ.ዳ.ና
    • መነሻ
    • ሁሉም ጽሑፎች
    • ሰንሰለት
    • ጎዳና

    ጎ.ዳ.ና
    ዓላማ መግለጫ

    ማህበራዊ ገጾች

    © 2025 ጎ.ዳ.ና . ሁሉም መብቶች የተጠበቁ ናቸው

    godana

    ጎዳና

    By Godana

    ጎዳና - ጋዜጣዊ መግለጫ

    በቅድሚያ የከበረ ሰላምታችን ይድረስ፥ እንኳን ወደ ጎዳና በሰላም መጡ!ጎዳናችን በበጎ ፈቃደኞች ተቋቁሞ የሚመራ፣ መሠረቱን ድረገጽ ላይ ያደረገ የብዙኅን መገናኛ መድረክ ነው።ጎዳናን ለመጠሪያነት ስንመርጥ የተነሳንበትን ዓላማ በአግባቡ እንደሚወክል በማሰብ ነው። ጎዳና ሰፊ መንገድ ነው፤ አንዱን ከአንዱ ሳይለይ መንገደኛውን ሁሉ የሚያስተናግድ፤ እንደቀጫጭን መንገዶች ለአቋራጭ ሳይሆን ለረጅም ጉዞ የሚመረጥ።ከዚህ አኳያ ነው ጎዳናችን አይነኬ የሚባል ርዕስ ሳይኖር ሀገራችንን ብሎም ትውልዳችንን ይረባሉ በተባሉ ሐሳቦች ላይ አካታች በሆነ፤ ለሥነ-ምግባር በመገዛት፤ በተለይም የተለያዩ ትውልዶችን የሚያሰናስል የውይይት መንገድ ለመፍጠር አልሞ የተነሳው።በአሁኑ ወቅትም እንደ ሀገር ብሎም እንደ ሕዝብ የተጋረጡብንን የፍትሕ፥ የሰብአዊነት እና የእኩልነት እጦት የወለዳቸውን ቀውሶች ለመጋፈጥ ብሎም በግለሰቦች እና በቡድኖች መካከል ያሉ ልዩ ልዩ ሐሳቦችን በበሰለ ውይይት እንዲንጸባረቁ መደላድል መፈጠሩ አንገብጋቢ መሆኑን ጎዳናችን አምኖ በቁርጠኝነት የበኩሉን ለማበርከት መጥቷል።ላሰብነው የነጻ ሐሳብ መድረክ ባለሐሳቦች ሐሳባቸውን በመግለጻቸው ምክንያት ብቻ የሚያጋጥማቸውን ስጋት በመረዳት፥ በቅድሚያ ለባለሐሳቦች አንጻራዊ ሰላም ያለበትን አውድ ፈጥረናል።በተጨማሪም ጎዳናችን አጋርነት (solidarity) ቁልፍ እሴቱ ነው። በመሆኑም ሰብአዊነት፥ ፍትሕ እና እኩልነትን የሚረዳ፣ የሚያከብር፣ የሚደግፍ ብሎም የሚያጠናክር ባህልን ለማስፈን እንተጋለን።በተለይም አዲሱ ትውልድ ከዛሬው እውነታ በዘለለ ከቀደምት ትውልዶች የሚማርበት፥ ምክንያታዊነትን የሚያጸናበት እንዲሁም በራሱ መንገድ የግል ብሎም የማኅበረሰቡን ሕይወት የሚያሻሽልበትን አማራጭ ማፈላለጊያ ለመሆን ጎዳና ቁርጠኝነት አለው።ይህንን በማስመልከትም በቀጣይ ሳምንት ይፋ የሚደረገው የመጀመሪያው ልዩ የውይይት አጀንዳችን - በዚሁ በያዝነው ወር 20 ዓመት የሞላውን ምርጫ 1997ን እና በታሪክ ጥሎ ያለፈውን ውጤት መመርመርን መርጧል።ይህ ልዩ የውይይት አጀንዳ ወሩን ሙሉ የተለያዩ አንጋፋ እንዲሁም በምርጫው በቀጥታ የተሳተፉ የፖለቲካ መሪዎች፥ ሂደቱን የተከታተሉ ግለሰቦች ብሎም በተመረጡ ጉዳዮች ላይ የሙያ ዕይታቸውን የሚያካፍሉ ግለሰቦች የሚሳተፉበት ይሆናል።የዚህ ልዩ እትም ዋና ዓላማ ታሪክን ከመንገር በዘለለ ጉዳዩን መለስ ብሎ በጥልቀት መመልከት በመሆኑ፣ ተሳታፊዎች እስከዛሬ በጉዳዩ ላይ ከሰጡት አስተያየቶች በዘለለ በጥልቀት ሂደቱን ገምግመዋል፤ ቀጣይ ትውልድ ቢማርባቸው ብሎም ቢያሻሽላቸው ባሏቸው ስህተቶች ላይም ምክራቸውን ተይበዋል።በዚህም መሠረት ጽሑፎቹ ከምርጫው በፊት የነበረውን ኹኔታ በጥልቀት የሚያስቃኙ እንጂ የ'ነበር' ታሪክ ጠቃሽ ብቻ አይደሉም።ጎዳናችን የእናንተን ሐሳብ የሚቀበልበትን መንገድም አዘጋጅቷል። ወደ ድረ ገጻችን በመሄድ በዚሁ ባነሳነው ጉዳይ ላይ ያላችሁን አስተያየት፣ ትውስታ ብሎም ሂደቱ ይዞት የመጣውን በጎ ወይም አሉታዊ ውጤት የዳሰሱ አጫጫር ጽሑፎችን ሊልኩልን ይችላሉ። እኛም ይዘቱን ፈትሸን በድረ ገጻችን ላይ እናትመዋለን።ጎዳና በቀጣይ በተለያዩ አምዶች ጠቃሚ የሆኑ ሐሳቦችንና ጉዳዮችን፣ ታሪኮችንና ነባራዊ ኹኔታቸውን የሚዳስሱ ሥራዎችን ከሕዝቡ ወስዶ ለሕዝቡ ያደርሳል። መወያያ፣ መነጋገሪያ፣ አንዱ በሌላው ጫማ ሆኖ የሚያይበትን አንጻር በመስጠት ይቀጥላል።እስከዛው የማኅበራዊ ገጾቻችንን በመከተል ይቆዩን! ጎዳናግንቦት 6፣ 2017 ዓመተ ምሕረት

    • Previous
    • 1
    • Next